Gibre Himamat መጽሐፈ ግብረ ሕማማት

የግብረ ሕማማት መጽሐፈ ፣ መጽሐፈ ጾመ ድጓ እና የአጽዋማት ምንባባት
የክርስቲያን፡ ወገን፡ የሆነ፡ ሁሉ፡ በየዓመቱ፡ ሰሙነ፡ ሕማማትን፡ ራሱን፡ ከፈቃደ፡ ሥጋና፡ ከክፉ፡ ነገር፡ ከልክሎ፡ በየቤተ፡ ክርስቲያኑ፡ በወያDግኘት፡ የሚተላለፉትን፡ መልእክታት፡ በመከታተልና፡ በመሳተፍ፡ በጾም፡ በጸሎት፡ በስግደትና፡ በአስተብርኮት፡ ይሰነብታል። 


የመሠረቱና፡ ታሪካዊ፡ አመጣጡም፡ ከአባቶቻችን፡ ቅዱሳን፡ ሐዋርያት፡ ተያይዞ፡ የመጣ፡ ነው። ይኸውም፡ ጌታችን፡ ኢየሱስ፡ ክርስቶስ፡ ከሙታን፡ ተለይቶ፡ ተነሥቶ፡ ለሐዋርያት፡ እየተገለጸ፡ እስከ፡ አርባ፡ ቀን፡ ድረስ፡ መጽሐፈ፡ ኪዳንንና፡ ሥርዓተ፡ ቤተ፡ ክርስቲያንን፡ ሲያስተምራቸው፡ ቈይቶ። በአርባ፡ ቀኑም፡ ሐዋርያትን፡ በአንብሮተ፡ እድ፡ ሹሟቸውና፡ ባርኳቸው፡ አርጓል። (ማር፡ ፲፮፡ ፲ህ። ሉቃ፡ ፳፬፤ ፶፩። የሐዋ፡ ሥራ፡ ፩-፱፡ )፡ 

ከዚህም፡ በኋላ፡ ሐዋርያት፡ በኢየሩሳሌም፡ ካሉ፡ ምዕመናን፡ ጋር፡ ጾም፡ መጾምንና፡ ትንሣኤውን፡ ማክበር፡ ጀመሩ። በዚህ፡ ጊዜ፡ በጽርሐ፡ ጽዮን፡ ተሰብስበው፡ በደነገጉት፡ የቤተ፡ ክርስቲያን፡ ሥርዓት፡ ፥ ስለ፡ ሰሙነ፡ ሕማማት፡ ወአንትሙሰ፡ ተዐቅቡ፡ ወግበሩ፡ ተዝካረ፡ ሕማማቲሁ፡ እናንተ፡ ግን፡ ጠብቃችሁ፡ የመከራ፡ መስቀሉ፡ መታሰቢያ፡ የሆነውን፡ ሕማማቱን፡ አድርጉ፡ አክብሩ፡ ሲሉ፡ አዝዘዋል። (ትእዛዝ፡ ፴፩)፡ 

ሆኖም፡ ሐዋርያት፡ ለስብከተ፡ ወንጌል፡ ይፋጠኑ፡ ነበረና፡ እንደ፡ ዛሬው፡ ሁሉ፡ ጊዜውን፡ አልወሰኑትም፡ ነበር። ከሐዋርያት፡ ቀጥለው፡ የተነሱ፡ ሊቃውንትም፡ ቢሆኑ፡ እንደዚሁ፡ በዐተ፡ ጾምን፡ ከጥር፡ ፲፩፡ ቀን፡ እስከ፡ የካቲት፡ ፳፩፡ ቀን፡ ከጾመ። በኋላ፡ ሰሙነ፡ ሕማማትን፡ ደግሞ፡ ከዐቢይ፡ ጾም፡ ለይተው፡ ከመጋቢት፡ ፳፪፡ እስከ፡ መጋቢት፡ ፳፰፡ ቀን፡ በመጾም፡ መጋቢት፡ ፳፱፡ ቀን፡ ትንሣኤውን፡ ያከብሩ፡ ነበር። ይህ፡ ሥርዓት፡ ሲያያዝ፡ እስከ፡ ድሜጥሮስ፡ ዘመን፡ ደረሰ። 


ከ፩፻፹፰፡ የሆቿ፡ እስከ፡ ፪፻፴፡ ዓ.ም፡ የነበረው፡ ሊቅ፡ ጳጳስ፡ ድሜጥሮስ፡ በአዘጋጀው፡ የጊዜ፡ መቁጠሪያ፡ (ባሕረ፡ ሐሣብ)፡ ስሙነ፡ ሕማማት፡ ከዐቢይ፡ ጾም፡ ቀጥታ፡ እንዲሆን፡ ተወስኖአል። ቤተ፡ ክርስቲያንም፡ በቀመረ፡ ድሜጥሮስ፡ ዓመታትን፡ በንዑስ፤ በማዕከላዊና፡ በዐቢይ፡ ቀመር፡ እየቀመረች፡ አጽዋማት፡ የሚገቡበትንና፡ በዓላት፡ የሚውሉበትን፡ ጊዜ፡ ለምዕመናን፡ ታሳውቃለች። 

ስለሆነም፡ የሰሙነ፡ ሕማማት፡ ሥርዓተ፡ ጸሎትና፡ አገልግሎት፡ ሁኔታ፡ ከቤተ፡ ክርስቲያናችን፡ ሥርዓተ፡ አምልኮት፡ ጋር፡ የተያያዘ፡ ቢሆንም፡ አሁን፡ ያለውን፡ ሥርዓት፡ የያዘ፡ ግብረ፡ ሕማማት፤ የተሰኘው፡ መጽሐፍ፡ ተዘጋጅቶ፡ በሥራ፡ ላይ፡ የዋለው፡ ከጌታ፡ ልደት፡ በኋላ፡ በ፲፬ኛው፡ ምዕት፡ ዓመት፡ ነው። 

ከ፩ሺ፫፻፵፡ እስከ፡ ፩ሺ፫፻፹፡ ዓ.ም፡ የነበሩት፡ ብፁዕ፡ አቡነ፡ ሰላማ፡ ብርሃነ፡ ዐዜብ፡ ከዐረብኛ፡ ወደ፡ ግእዝ፡ እንደተረጎሙት፡ ቀደም፡ ሲል፡ በግእዝ፡ ብቻ፡ ታትሞ፡ በነበረው.፡ የግብረ፡ ሕማማት፡ መጽሐፍ፡ ውስጥ፡ ተገልጦአል። 

የመጽሐፉ፡ ስያሜም፡ ከጥንተ፡ ስሙ፡ ጀምሮ፡ ግብረ፡ ሕማማት፡ እንደሚባል፡ በመጽሓፉ፡ ውስጥ፡ በብዙ፡ ክፍል፡ ተጠቅሶ፡ ይገኛል። ለዚሁም፡ በቂ፡ የሆነ፡ ምሥጢራዊ፡ ምክንያት፡ እንዳለው፡ ይታመናል። ሊቀ፡ ነቢያት፡ ሙሴ፡ በቀዳሚ፡ ገብረ፡ እግዚአብሔር፡ ሰማየ፡ ወምድረ፤ በመጀመሪያ፡ እግዚአብሔር፡ ሰማይንና፡ ምድርን፡ ፈጠረ፡ (ዘፍ፡ ፩፡ ፩)፡ ያለውንና፡ ነቢዩ፡ ዳዊት፡ ዘገብረ፡ ሰማያተ፡ በጥበቡ፡ ሰማያትን፡ በጥበቡ፡ የሠራ፡ (የፈጠረ)፡ እግዚአብሔር፡ ቸር፡ ነውና፡ አመስግኑት። (መዝ፡ ፻፴፭፡ ፭)፤ ሲል፡ እንደተናገረው፡ ቀዳማዊ፡ ቃል፡ እግዚአብሔር፡ ወልድ፡ በጥንተ፡ ፍጥረት፤ ከባሕርይ፡ አባቱ፡ አብ፤ ከባሕርይ፡ ሕይወቱ፤ መንፈስ፡ ቅዱስ፡ ሕልው፡ ሆኖ፡ በረቂቅ፡ ጥበቡ፡ ዓለማትንና፡ ፍጥረታትን፡ ሁሉ፡ በየወገኑ፡ ፈጥሮ፡ እንደየባሕርያቸው፡ በቸርነቱ፡ መግቦና፡ ጠብቆ፡ የሚኖር፡ እንደመሆኑ፡ ሁሉ፡ በኋላ፡ ዘመንም፡ ራሱ፡ አካላዊ፡ ቃል፡ ወልድ፡ በተለየ፡ አካሉ፡ ዓለምን፡ ከፈጠረበት፡ አዳምን፡ ከነዘሩ፡ እንደገና፡ መልካታል፤(፪ኛ፡ ቆሮ፡ ፫፡ ፲፯። ራዕ፡፳፩፡፭፡ ኢሳ፡ ፵፫፤፲፱)፡ 

ሊቁ፡ ዮሐንስ፡ አፈወርቅም፡ ይትባረክ፡ እግዚአብሔር፡ ዘሰመየ፡ ሕማማተ፡ ወልዱ፡ ወስብሐት፡ የልጁ፡ ኢየሱስ፡ ክርስቶስን፡ ሕማማት፡ ክብርና፡ ምሥጋና፡ ጌትነት፡ ብሎ፡ እግዚአብሒር፡ ይክበር፡ ይመስገን፡ ያለው፡ ስለዚህ፡ ነው። 

ምሥጢራዊ፡ ዓላማውም፡ ጌታ፡ በሕማሙ፡ ሕማማችንን፤ በሞቱ፡ ሞታችንን፤ በትንሣኤው፡ ዘለዓማዊ፡ ነፃነትንና፡ ክብርን፡ ያጐናጸፈን፡ መሆኑን፡ ከማስገንዘቡም፡ በላይ፡ በባሕርዩ፡ መከራና፡ ሞት፡ የሌለበት፡ ሕያወ፡ ባሕርይ፡ አምላክ፡ መሆኑ፡ በሰሙነ፡ ሕማማት፡ በየአንዳንዱ፡ ቀን፡ ይነበባል፡ ይተረካልም። 

መጽሐፈ፡ ምሥጢረ፡ ሥጋዌን፡ ነገረ፡ መስቀልን፡ ምሥጢረ፡ ቍርባንንና፡ ምሥጢረ፡ ትንሣኤ፡ ሙታንን፡ የያዘ፡ እጅግ፤ ጥልቅና፡ ምጡቅ፡ ስለ፡ ሆነ፡ በየጊዜው፡ በብራና፡ እየተጻፈ፡ ሲሠራበት፡ ለ፮፻፤ ዓመታት፡ ያህል፡ ከኖረ፡ በኋላ፡ በ፲፱፻፵፪፡ ዓ.ም.፡ በመምህር፡ ወልደ፡ ሚካኤል፡ ብርሃነ፡ መስቀል፡ (ብፁዕ፡ አቡነ፡ ሉቃስ)፡ አቅራቢነት፡ በብፁዕ፡ ወቅዱስ፡ አቡነ፡ ባስልዮስ፡ ፈቃድ፡ ታትሞ፡ ለአብያተ፡ ክርስቲያናት፡ ሁሉ፡ እንዲዳረስ፡ ተደርጎአል። የመጀመሪያው፡ እትም፡ ስለ፡ አለቀ፡ እንደገና፡ ለሁለተኛ፤ ጊዜ፡ ከ፴፡ ዓመት፡ በኋላ፡ በ፲፱፻፸፪፡ ዓ.ም.፡ በብፁዕ፡ ወቅዱስ፡ አቡነ፡ ተክለ፡ ሃይማኖት፡ ፈቃድ፡ በግእዝ፡ ብቻ፡ ታትሞ፡ በሥራ፡ ላይ፡ እንዲውል፡ ሆኖአል። ይሁን፡ እንጂ፡ አገልግሎቱ፡ ምዕመናንን፡ ስለ፡ አላሳተፈ፡ የተሟላ፡ አልነበረም። 


በአሁኑ፡ ጊዜ፡ አብዛኛው፡ ሕዝበ፡ ክርስቲያን፡ በሚሰማው፡ በአማርኛ፡ ጭምር፡ ቢታተምና፡ ቢቀርብ፡ አገልግሉቱ፡ የበለጠ፡ እንደሚሆን፡ ስለታመነበት፡ በሊቀ፡ መዘምራን፡ ላዕከ፡ ማርያም፡ ወ/ኢየሱስ፡ በግእዝና፡ በአማርኛ፡ ተዘጋጅቶ፤ በሊቃውንት፡ ጉባዔ፡ ተመርምሮ፤ በብፁዕ፡ ወቅዱስ፤ አቡነ፡ ጳውሎስ፡ ፓትርያርክ፡ ርእሰ፡ ሊቃነ፡ ጳጳሳት፡ ዘኢትዮጵያ፡ ሊቀ፡ ጳጳስ፡ ዘአክሱም፡ ወዕጨጌ፡ ዘመንበረ፡ ተክለ፡ ሃይማኖት፡ መልካም፡ ፈቃድ፡ ለመጀመሪያ፡ ጊዜ፡ በግእዝና፡ በአማርኛ፡ እንዲታተም፡ ተደርጎአል። 

በዚህ፡ መሠረት፡ የሰሙነ፡ ሕማማት፡ ጸሎትና፡ አገልግሎት፡ ጠቅላላ፡ ሥርዓት፡ በዚህ፡ መጽሓፈ፡ ግብረ፡ ሕማማት፡ በየክፍሉ፡ ተጽፎ፡ ስለሚገኝ፡ ካህናትም፡ ምዕመናንም፡ መጽሐፉን፡ በመያዝ፡ ሥርዓቱን፡ ለመከታተል፡ ያመቻል፡ የሚል፡ ጽኑእ፡ ተስፋ፡ አለን። 

በግእዝና፡ በአማርኛ፡ ተዘጋጅቶ፡ መቅረቡ፡ በተለይ፡ ምዕመናንና፡ ምዕመናት፡ ጸሎቱን፡ በትጋት፡ እንዲካፈሉ፤ ትምህርቱን፡ እንዲከታተሉ፡ ምሥጢሩንም፡ እንዲያስተውሉና፡ በረከቱን፡ እንዲሳተፉ፡ ከማስቻሉም፡ በላይ፡ መሪያቸው፡ ኢየሱስ፡ ክርስቶስን፡ በፍጹም፡ እምነትና፡ ፍቅር፡ እንዲከተሉ፡ ጥሪውን፡ ያስተላልፋል፡ ይቀሰቅሳል። ቅዱስ፡ ጴጥሮስም፡ ለዚህ፡ ተጠርታችኋል፡ ክርስቶስም፡ እኮ፡ ፍለጋውን፡ ትከተሉ፡ ዘንድ፡ ምልክቱን፡ ሊተውላችሁ፡ ስለ፡ እናንተ፡ መከራ፡ ተቀብሎአል፡ ያለው፡ ስለዚህ፡ መሆኑን፡ ያስታውሰናልና፡ ነው። (፩ኛ፡ ጴጥ፡ ፪፡ ፳፪።)፡

0 Comments